Monday, May 7, 2012

ብላሽ ታሕሪር -(የተበላሸው ነፃነት!)

 

ብላሽ ታሕሪር -(የተበላሸው ነፃነት!)(አሳዛኙ የኤርትራዊያኖቹ ታሪክ)

ትንታኔ እና ትርጉም ጌታቸው ረዳ www.ethiopiansemay.blogspot.com getachre@aol.com
from the Editor: In order to read the fonts bigger you can use your keyboard Ctrl and + sign as desire to resize the fonts.

ማስገንዘቢያ፤-
መጽሐፉን ለሚያነብቡ የትግርኛ አንባቢዎች ማሳሰቢያ   
ከደራሲው መጽሐፍ ውስጥ የተዘገበው “ኢሳያስ እና በዙርያው ያሉት ባለስልጣኖች ሁሉ” ትውልድ ሐረጋቸው ‘ከኢትዮጵያ/ትግራይ ስለሆነ፤ ለወንጀላቸው ተጠያቂነት የትውልድ ሐረጋቸው ከተገኘው ባሕሪ እንደሆነ እና ኤርትራዊ  ደም ስለሌላቸው በሕዝቡ ላይ ባዕዳዊ የጭካኔ ስርዓት መስርተዋል’፡ ሲል ለመጥፎ ስራቸው ለኢትዮጵያ ያለው ጥላቻ እና የተሳሳተ ግንዛቤ ስያንጸባርቅ ታነባላችሁ። በደራሲው የተሳሳተ ያልበሰለ አመለካከት ፤ እነ ኢሳያስ እነ የማነ እና ሐጐስ ክሻ ….ኤርትራዊያን ቢሆኑ ኖሮ “ኤርትራ” የምድር ገነት ትሆን ነበር” ማለት አምባገነንነት በሐረግ ፤በትውልድ የሚመጣ እንደሆነ የሚገልጸው ምክንያት ኤርትራ ስለ ኢትዮጵያ ያላቸው ጥላቻ እና የተሳሳተ አመለካከት  ምን ያህል ስር እንደሰደደ ነው።  ስለዚህ ያንን እንደተጠበቀ ሆኖ የሚከተለውን  በጥሞና አንብቡ።

የዛሬ መነጋገሪያችን አምና ያቆምኩትን ከትግርኛ መጻሕፍት ዓለም ትንተና አምድ እንድቀጥል ያስገደደኝን ሰሞኑን አንድ አስደናቂ የትግርኛ መጽሐፍ ያነበብኩትን በጨረፍታ ላካፍላችሁ ነኝ።  ትልሚ ንዘርኢ ክርዳድ (እቅድ ለአረም እርሻ) ወይንም ( እንክርዳድ የመዝራትን እቅድ ያስከተለው ሰበብ) በሚል ርዕስ የሻዕቢያው ኢሳያስ አፈወርቂ ሳሕል ተራራ በ1973 ዓ.ም (በፈረንጆች አቆጣጠር) “መንካዕ” (የሌሊት ወፍ) በሚል ርዕስ ኢሳያስ ተቀናቃኞቹን ለማስወገድ የጻፋት፤ እስከዛሬ ድረስ ብዙ ሰው ያላነበባት እና ይፋ ያልወጣች ከግል ሻንጣው ወደ ግል ሻንጣው ከመሸጋገር በስተቀር ሌላ ቦታ አንዲቀመጥ ያልተፈቀደ ኢሳያስ እራሱ የጻፋት ያታሪካዊ የድርጅቱ መጽሐፍ ጋር ተደምሮ በጠቅላላ  ወደ 622 ገጽ የያዘ የኢሳያስ አፈወርቂ ማንንትን የሚገልጽ መጽሐፍ ነው በጨረፍታ የማሳያችሁ።
ድርጅቱ ወንጀሎች፤እንዲሁም የድርጅቱ ታጋዮች ስቃይ እና ኤርትራኖች ለመገመት የሚያስቸግር መስዋእትንት እና መከራ ተቀብለው ያገኙትን “ነፃነት” ውጤቱ አሳዛኝ እና የሲኦል ምድር ሆና፤ ኤርትራ የኢሳያስ እና የጥቂቶች ንብረት እንዴት ሆና እንደቀረች፤ እንዲሁም  ሕዝቡ ያልጠበቀውና አይቶት ወደ የማያዉቀው ስቃይ እንዴት እንደተዳረገ “አለና” (አለን) በሚል የብዕር ስም የሚጠራው የድርጅቱ ታጋይ የነበረ አቶ ረድኢ መሓሪ የተባለ ኤርትራዊ የጻፈው ይህ ልብ የሚሰርቅና የሚያሳዝን የትግርኛ መጽሐፍ የትግርኛ ትግርኛ የሚያነቡ ሰዎች እንዲያነቡት እጠቁማለሁ።
መጽሐፉ በኤርትራ ታጋዮች ላይ የተሰነዘሩ ሦስት የኢሳያስ የእልቂት ዘመቻ እቅዶችን (1) መንካዕ (2)የሚን (ቀኝ አክራሪ ክንፍ) (3) G15 (ከባድሜ ጦርነት ወዲህ “የጥገና ለውጥ” ስለጠየቁ ኢሳያስ ያሰራቸው 15 የድርጅቱ ከፍተኛ መሪዎችና የኢሳያስ የጭካኔ እርምጃ በማውገዝ ያጋልጣል። በዚህ ድረገጽ የተጻፉ የዘመን አቆጣጠሮች ደራሲው በተጠቀመው በአውሮጳዊያን ዘመን ነው።
መጽሐፉ ለገበያ ከወጣ በጣም ሁለት ወሩ  ነው። መጽሐፉ የተላከልኝ ከቅርብ ወዳጄ ሲሆን፤ መጽሐፉ ከጀመርከው እንደትጨርሰው የሚያስገድድ ማራኪ የአጻጻፍ ስልት እና ለሕሊና የሚከብዱ የድርጀቱ መሪዎች እና የኢሳያስ ባሕሪዎች እና ግፎችን እያሳዘነም ቢሆን ያሳያል። ለአማርኛ አንባቢ እንዲመች እራሴ “ርዕስ እየሰጠሁ’  በጥቅስ እያሳየሁ የማስንብባችሁ መጽሐፉ ለመጀመሪያ ጊዜ የኤርትራ መሪዎች አስከፊ ገጽታ እና ታሪካቸው ካሁን በፊት በማንኛውም ሰነድ ተጽፎ ወይንም ተነብቦ የማያውቅ ውስጣዊ ጓዳቸውን ጎርጉሮ ያጋለጠ መጽሐፍ ነው።መጽሐፉ ካነበብኩት በሗላ የተሰማኝ ቁጭት “የወያኔ ትግራይ” ታጋዮች (ለማጋለጥ ከመኮሩ ጥቂቱ ታጋዮችን አይመለከትም- ምስጋና ይድረሳቸው) ምነው እንደዚህ ጸሐፊ በሆኑልን? የሚል ቁጭት እና ንዴት ነበር የተሰማኝ።
ደራሲው  “ሻዕቢያ” ወይንም በትግርኛ አጠራሩ “ህዝባዊ ግምባር” ተብሎ በሚጠራው የኤርትራ ነፃ አውጪ ድርጅት ውስጥ  ከ1974 ዓ.ም ታጋይ የነበረ ነው። ድርጅቱ ውስጥ በቆየበት በርካታ አመታት፤ ብዙ አሰቃቂ ጦርነቶችን ተካፍሏል። በሺዎቹ አ’ሰልፎ ለኤርትራ  ኗሪዎች ነፃነትና መብት አጐናጽፋለሁ ብሎ ወደ ጫካ እና ሳህል ተራራ የገባው ሻዕቢያም ቢሆን የኤርትራዊያን መብት ተጋፍቷል ተብለው “ባዕድ ገዢዎች” ተብለው በኤርትራዊያን ከሚከሰሱት ስርዓቶች በባሰ መልኩ የታጋዮች እና የኗሪዎች መብት በሳዛኝ መልኩ በጫካ አስተዳደሩም ሆነ ወደ መንግስትነት ደረጃ ከተለወጠ በሗላም ብልሹ እና አረመኔዊ አስተዳደሩ በመቀጠል የኤርትራ ሕዝብ ከመቸውም ጊዜ የከፋ አሳዛኝ ሕይወት እየኖረ እንዳለ ደራሲው በዓይኑ ያያቸው፤በሕሊናው ለአመታት የዘገባቸው ትዝታዎቹ እና ድርጁቱ ከተመሰረተ ጀምሮ እስከ አሁን ድረስ በመሪነት የሚገኘው አምባገነኑ የኢሳያስ አፈወርቂ ብልሹ የአመራር ውጤት ኤርትራ አሁን ወዳለችበት በዓይነስውርነት ወደ እምትራመድበት አሳዛኝ ታሪኳ እንዴት እንደገባች ግልጥልጥ አድርጐ በመጽሐፉ ውስጥ አስፍሮታል።    
በደራሲው አዘጋገብ የኤርትራ ነፃነት ወደ አሳዛኝ ፍጻሜ መድረስ የመጀመሪያው ተጠያቂ ያደረገው የአሁኒቷ ኤርትራ መሪ ኢሳያስ አፈወርቂን ሲሆን፤ ለሰውየው አምባገነንት ቀጣይ መንገድ ጠራጊዎች አብረውት ሲያጫፍሩ የነበሩትን ድርጅቱን የለቀቁ  አመራሮችና አንዳንድ ምሁራን እንዲሁም አሁንም አብረውት በመከተል ያሉ “ምሁራን” ተብየዎች እና የድርጅቱ ከፍተኛ ወታደራዊ አዛዦች ከኢሳያስ ባልተናናሰ በማውገዝ ተጠያቂ ያደረጋቸዋል።
ደራሲው የኢሳያስ ባሕሪ ምንነት፤የስልጣን ጥመኝነት ሲገልጽ በሎሌነት የሚያያቸው የያንዳንዱ ምኒስተሮቹ ባሕሪ እና የስልጣን ብልግና በዝርዝር በስም እየጠራ ሕዝቡ እንዲገነዘብ አድርጓል።
ኢሳያስ ከባድ የመጠጥ ሱሰኛ እንደሆነ እና በመጠጥ ሃይል ሲሸነፍ አብረውት የሚያጣጡትን ሚኒስትሮቹን እና ጀኔራሎቹን በጥፊና በእርግጫ ሲደበድባቸው፤ በድብደባው ምክንያት በአካላታቸው ከባድ ጉዳት ሲደርስባቸውም ወደ ውጭ አገር በመላክ ምስጢራዊ ሕክምና እንደሚደረግላቸው ይገልጻል።የተደበደቡት ከፍተኛ የወታደራዊ እና ሲቪል ባለማዕረጎችም በስም ዝርዝራቸው አስቀምጦታል።  
እንደምታስታውሱት በየጊዜው ሳይሰለቸኝ የትግራይ ምሁራንም ሆኑ የወያኔ ትግራይ ታጋዮች የሚያውቁትን የወያኔ መሪዎች የገበና ማሕደር እና ድርጅቱ በሕዝቡ ላይ ያደረሰው መከራ እስካሁን ድረስ ያልተገለጠ ምስጢር ለታሪክ እንዲያስመዘግቡ ደጋግሜ ብጠይቅም፤ እስካሁን ድረስ በጣት የሚቆጠሩ ጥቂት ታጋዮች ወደ ፊት በመምጣት የሚችሉትን ለማጋለጥ ሞክረዋል። እነዚህ ምስጋና የሚገባቸው ቢሆንም ከሻዕቢያ ባልተናናሰ ብሔራዊ ወንጀል እና ሰብአዊ መብት የጣሰ ወያኔን የሚያክል  ወንጀለኛ ድርጅት ብዙ ታጋዮች ካሁን በፊት ካነብብናቸው ምስጢሮች በበለጠ በብዙ መቶዎች የሚወጡለት መጽሐፍ ታትሞ ለታሪክ በተመዘገበ ነበር። አለመታደል ሆኖ አሁንም  ለእኛ ባልገባን ምስጢር ሚስጢሮቹን በየጓዳቸው እና በየልባቸው አፍነው በመያዝ “የወንጀላቸው ተባባሪዎች ሆነዋል” (ይህ በጥቅስ የጠቀስኩት ቃል ከአመታት በፊት ተጠቅሜ በመጻፌ ከወያኔዎች ወቀሳ/ስድብ በኢመይል ድረሶኝ እንደነበር ትዝ ይለኛል)።
በቅርቡ እንደ አቶ ረድኢ መሓሪ የመሳሰሉ በርካታ ኤርትራኖች ባስደናቂ ሁኔታ ኤርትራኖች ባልተጠበቀ ጊዜ የድርጅታቸውን ምስጢሮች ለህዝብ ይፋ በማድረግ ቁጭታቸውን ለታሪክ በማስመዝገባቸው አብዛኛው የኤርትራ ህዝብ የልቡን ነግረው ቅቤ እንዳጠጡት/እንዳሰደሰቱት ሁሉ ለእኛም ለኢትዮጵያዊያንም በቅርቡ ከወያኔ ታጋዮች በተመሳሳይ የወያኔ መሪዎች የተደበቁ ወንጀሎች እና ብልሹ አስተዳደራቸውና ባሕሪያቸው እንዲያጋልጡ አሁንም እንማጠናለን።
ደራሲው አቶ ረድኢ መሓሪ እንዳለው “የተደበቁ የህ.ግ.ደ.ፍ አመራር ቡድን ምስጦር እና ወንጀል መናገርና መጻፍ ለሚቀጥለው ትውልድም ሆነ አሁን ያለው ወጣት ትውልድ ማስተማርና ማሳወቅ የሚያስፈልገው ወቅቱ አሁን ገና አመራሩ ከስልጣን ከመወገዱ በፊት ነው።”
“የኢሳያስ አፈወርቂ ገበና የምናውቀው ብዙ አለ፤ ነገር ግን ደህና ጊዜ አለን፤ቀስ ብለን፤ረጋ ብለን እናደርገዋለን ብለው ምስጢሮችን ቀብረውት የሚገኙ ሰዎች ውሳኔአቸው የተሳሳተ መሆኑን ላስገነዝባቸው እወዳለሁ። ምክንያቱም ገና በመቀጠል ላይ ያለ የተቀበረው የኢሳያስ አፈወቂ መርሃ ግበር፤ ተንኰል እና ምስጢር አፍራሽ እንጂ ገምቢ ባለመሆኑ፤በመዳፉ ስር ተጨፍልቆ በባርነት ቀምበር የተያዛው ሕዝብ ላይ ተጨማሪ ጥፋት ከማውረዱ በፊት ለማስቆም ይረዳል።ከስልጣን ሳይወገድ በቁሙ ምስጢሮቹና ወንጀሎቹን  እንደነቃንበት እንዲያውቅልን እና አሞኝቶን እንዳልሄደ እሱም እንዲያውቀውና ሓፈረት ምን መሆኑን የሚያውቅ ከሆነ  “አታላይ ሕሊናው  ውስጥ ሰርጾ እንዲሸማቀቅ ይረዳል።” ይላል ደራሲው። ስለሆነም ወያኔዎችም ከኤርትራው ደራሲ ድፍረት እና እውነት በመመለክት አርአያነቱን እንደሚቀስሙ ተስፋ አለኝ።
የሆኖ ሆኖ ኤርትራኖች በቅርቡ ሰምተነው የማናውቀው ታሪክ ይፍ እያደረጉ ነው። ከዚህ ጻሃፊ ማለት /አለና/(ከአቶ ረድኢ መሓሪ) ሌላ ሰሞኑን “ፓይለት” በሚል የብዕር ስም በፓልቶክ እና በየሬዲዮኖቻቸው በጣም አስገራሚ ሰነድ ይፋ እያደረገ ነው። ሌላው የጂ 15 የተባሉት እስረኞች ጠባቂ የነበረም ብዙ ምስጢሮችን በቢሲ ዜና ማሰራጫ ማጋለጡ ይታወሳል።
ለዛሬ የአቶ ረድኢ መሓሪ መጽሐፍ “ትልሚ ንዘርኢ ክርዳድ” (እንክርዳድ የመዝራት እቅድ) ከሚለው መጽሐፍ የሰፈሩ አሳዛኙ የኤርትራ ማሕደር ላስነብባችሁ።
የኢሳያስ አፈወርቂ እናት ወ/ሮ አረጋሽ  ከረን ከተማ ቡና ቤት በሰራተኛነት ተቀጥረው ሲሰሩ ከየመናዊ ዜጋ እንዳረገዙት እና በምስጢር ግን በወላጅ አባትነት የሚታወቁት አባቱ አቶ አፈወርቂ ሆኖ እንዲያድግ እንደተደረገ በወሬ ደረጃ ከሚታሙ የኢሳያስ ማንንት “የሚነገሩ ሚስጥራዊ ወሬዎች”  በማለት በወሬ ደረጃ ደራሲው ጥቂት ዝርዘሮችን በማስፈር የሰማውን የኢሳያስ ማንነት ጽሑፉ ይጀምራል ።
ያም ባይሆን በሁለቱ ወላጆቹ የትግራይ ሰው እንደሆነ እና የባዕድ ባሕሪው ኤርትራን እየቀጠቀጣት ያለ ትከሻው ላይ ትንሽ ተራራ ያበቀለ የዘመናችን አምባገነን “ኤርትራዊ ቦካሳ” ነው ይለዋል። አለፍ ብሎም “ሰንደቃላማ የተከለ ሽፍታ” በማለት  ይጠራዋል። በዚህ የስልጣን ጉጉቱ ወደር የሌለው ሰው በመሆኑ ወደ ስልጣን ለመውጣት  ከ295 የታወቁ መካከለኛ እና ከፍተኛ ምሁራንን ገድሏል። እሺ ብለው ሲታዘዙት የነበሩትና የሚለውን የሚደግሙ “ፓፓጋሎ” (‘ተናገሪ ወፎች’ ይላቸዋል ደራሲው በጣሊያንኛ ቋንቋ) የሆኑ ታዛዦቹ እና በትግሉ ወቅት በረሃ ያልነበሩ ነገር ለቅላቂ እና ተሞዳሟጅ ኤርትራዊያን ከውጭ በማስመጣት ኤርትራን “ነፃ አገር” ብሎ ከመሰረተ በላ ኤርትራ በኢሳያስ ስር የታየው ጉድ እንዲህ ያቀርበዋል።
ርዕሶች ለአማርኛ አንባቢ እንዲመች የኔው ሲሆኑ ታሪኮቹ ግን ከመጽሐፉ ውስ  የተገኙ የደራሲው  ጽሑፎች ናቸው።

የድርጅቱ የጭካኔ ባሕሪዎች

ኢሳያስ ስታሊናዊ ባሕሪ ስለነበረው ነፃነት እና መብት አስገኛለሁ ብሎ ትግሉን በተቀላቀለ ታጋይ ላይ በኢሳያስ የመነፅር ክትትል ውስጥ ነበር። በሰዎች ላይ ቅጣት ሲፈጸም የጭካኔው ብዛት “የጀርመን ናዚዎች ሲደርጉት እንደነበር ሁሉ ሰዎች ዳቦ መጋገርያ/ፎረኖ ውስጥ  ይጠበሱ ነበር፤ እንደ ዶሮ የፈላ ውሃ በሰውነታቸው ላይ ተደፍቶባቸው ይገሸላለጡ ነበር፤ ሰዎች ከዛፍ ግንድ ጋር ታስረው ወተት በላያቸው ላይ እንዲፈስባቸው ይደረግ ነበር (በትንኝ እና ዝምብ እንዲወረር)። ይህ ድርጊት በዓይኑ ያላየ ሰው ለማመን የስቸግረው ይሆናል፤ ነገር ግን ተደርጓል። እንሆ ወንጀለኛው ኢሳያስ ከ1970 ዓ.ም (ፈረንጅ አቆጣጠር) እስከ 1991፤ በ20 ዓመት የትግል ወቅት ውስጥ ከ290 የታወቁ ምሁራን እንደፈጀ ከነስም ዝርዝራቸው የተመዘገበ እውነታ ነው።

እጸ ፋሩስ

ከነፃነት በፋጌና በተባለ አካባቢ ሰፊ መሬት በማልማት ሓሺሽ/እፀ ፋሩስ በማብቀል በዲፕሎማሲ ሻንጣዎች ወደ መካከለኛው ምስራቅ፤ናይጀሪያ፤ኬኒያ ወደ የራሱ ዲፕሎማቶቹ በመላክ አሰራጭ ቡድን በማደራጀት በሕገወጥ ዶላር ለማግበስበስ ለገበያ ይሸጣል።
ለማማን በሚያስቸግር ባሕሪ ዓለም ሕጋዊ አገርነቱን አውቆለት የተባበሩት መንግስታት መዝግቦት ሰንደቅ ዓለማ የሰቀለ መንግስት፤ካለ ህግደፍ በቀር እህል እንዳይሸጥ ብሎ ነጋዴን በጥብቅ እየተቆጣጠረ እና ቢፈቅድም ነጋዴው ኪሳራ ውስጥ  እንዲገባ እያደረገ፤ እራሱ ግን የሓሺሽ አዝመራ እየሰበሰበ ይሸጣል። በከበሩ ሉል ድንጋዮች፤ አልማዝና ወርቅ የመሳሰሉ ከዚህም ከዚየም ከያገሩ በመሰብሰብ በጥቁር ገባያ ውስጥ ንግዱን ያጧጡፋል፤የጦር ሕገ ወጥ መሳሪያዎችን በማዟዟር ዶላር ይሰበስባል፤ከባሕር ጠለፋ አሸባሮወች ጋር በመተባበር የንግድ መርከቦችን በጠለፋው ሂደት ተሳትፏል። እንደዚህ ያለ አስገራሚ ሽፍታ “መንግስት” ታይቶም ተሰምቶም በታሪክ አይታወቅም።

የአማርኛ ሙዚቃ

ኤርትራ ውስጥ የአማርኛ ሙዚቃ እንዳይደመጥ በሕግ ተከልክሎ ነበር። በየሙዚቃ መሸጫ መደብሮች ውስጥ የነበሩ የአማርኛ ሙዚቃ ካሴቶች፤ሲዲዎች እና ቪዲዮዎች በዘመቻ እንዲሰበሰቡ ተደረገ። አማርኛ ሙዚቃን ያዳመጠ ወይንም ያዳመጠች ከባድ ቅጣት እንደሚደርስባት ማስጠንቀቂያ ተላለፈ። የተገላቢጦሽ በህግደፍ ባለስልጣኖች መኪና ውስጥ የሚደመጡ ሙዚቃዎች ግን የአማርኛ ሙዚቃ እንጂ የትግርኛ ሙዚቃ አልነበረም። (ይህ ዜና እኔም በዳድሜ ጦርነት ውቅት ወይንም ከዛ በፊት ይመስለኛል ሃዋሪያ ጋዜጣ ከኤርትራ ጋዜጣ አንባቢ አምድ ውስጥ ያገኘሁትን ተርጉሜ አቅርቤው ነበር ፤ ጌታቸው ረዳ)
ይህም ሆኖ፤ ከወደ ማመሺያው ከሰዓት በላ ግን በየመአዝኑ የአማርኛ ሙዚቃ ሲለቀቅ የካቴድራለ እና ጎዳና ሓርነት (ኮምብሽታቶ) አካባቢ ወደ አዲስ አበባነት ይቀየራሉ። ዛሬ ግን “ቲቪ ኤሬ” የሚያስተላልፈው ዜና አንድ ነገር ለአስር አመት ሳይሰለች እየደጋገመ ውሸት እና የቸከ የካቢኔ ሚኒሰትሮች ደባራ ዘገባ እያስተላለፈ የሕዝቡን ጀሮ ስላሰለቸው፤ ሕዝቡ አሰልቺውን ውሸት ከማዳመጥ ይልቅ “ሽንግርዋ” በመባል የሚታወቀው የድምጻውያን ውድድር መዝናኛ ክፍለጊዜ ማየት እና ማዳመጥን መርጧል።

ብላሽ ታሕሪር (የተበላሸው ነፃነት)

1-     ቤተክርስትያን እና መስጊድ በለማኞች የተጥለቀለቀ ነው። ረሃብ የፈጠረው እምባ ከህፃናቱ  ዓይን አንደ ውሃ ሲወርድ አንጀት ይበላል። የወላጆች ትላልቅ ውብ ዓይኖች ተሟጠው ወደ ውስጥ ገብተው ጉድጓድ ሰርተዋል። የሙሽሮች ውብ  አገጫቸው ወደ ውስጥ ተሰርጉዶ አጥንታቸው ወደ ውጭ አሞጥሙጦ  ይታያል።ምን የመሰለ ቀጭን ነጭ ጋቢ ጣል አድርገው የለበሱ፤ ሌሎችም በጥቁር ሻሽ ፊታቸው የሸፈኑ ክርስትያን እና እስላም ውብ ወጣት እህቶቻችን እና እናቶች በሃፍረት እራሳቸውን ላላማሳወቅ ተሸፋፍነው በየጐዳናው ሲለምኑ ይታያሉ።
2-    ሴቶች ታጋዮች ወደ አስነዋሪ የጎዳና ስራ  በሴት አዳሪነት መተዳደር ተሰማርተዋል። ነባር ተጋዮች የመለመኛ ፈቃድ አውጥተው “እርዱን” የሚል ጽሑፍ በመያዝ በአስመራ እና በሌሎች ከተሞች መታየት ጀመሩ።  ከ1994 እስከ 2007 በአስራ ሦስት አመት ውስጥ በ1991 ዓ.ም ነፃነት ታውጆ በድል የገባ 100 ሺሕ ታጋይ፤ አብዛኛው ተወግዷል፤ዳግም ለሁለተኛ ዙር ለስደት ተዳርጎ ተሰዷል። ባጠቃላይ 95ሺህ ማለት ይቻላል በዚህ ሁኔታ የተሰናበተ ነው።በ1993 እስከ 1995 መልሶ ያቋቋማቸው ታጋዮችም እራሱ በለኰሰው የባድሜ ጦርነት፤ በተከታታይ ከኢትዮጵያ ጋር ያደረገው 3 ትልልቅና ከባድ ጦርነቶችና እንዲሁም ወደ ሶማሊያና ሶዳን የላካቸው ተዋጊዎች አብዛኛዎቹ አልቀዋል።  ስለዚህም ኤርትራ ነባር የህ.ግ ተዋጊ  አላት ብሎ ደፍሮ መናገር አይቻልም።
3-     ታጋዩ መስዋእት ከፍሎ መጨረሻ ላይ ያገኘው አሰዛኝ ውጤት ግን “ኢሳያስን በወርቅ መንበር አስቀምጦ እራሱን ወደ ልመና ማሰማራት ነበር”። አሳዛኙ ሁኔታ ለመግለጽ ዘፋኙ ተኽለንኪኤል ገብረ(ወዲ ገብሩ) የሚከተለውን ግጥሞ  ዘፍኗል።
“ደሞዞም ክልተ ሚኢቲ
ድራሮም ሽሕ ንሓንቲ ለይቲ፡
ገለ ዊስኪ ቀጢኑዋ
ገለን ባኒ ጨኒቑዋ፡
(ሁለት መቶ ደሞዛቸው
አንድ ሺሕ ብር የሚያጠፉ ለራታቸው።
አንዱ ዊስኪ ቀጠነብኝ ይላል፤
ሌላው ዳቦ አርሮበታል፡ ባይኑ ማየት ተስኖታል።) በማለት የተገኘው የኢሳያስ የነፃነት፤ ስርዓተ ባዶነቱን በሚገባ ገልጸታል። ይላል ደራሲው።

የቤተክርስትያናትና የገዳማት የተቸረ ስጦታን በሚመለከት

ከምእመናን የሚገኝ ለቤተክረስትያናት እና ገዳማት መገልገያ የተሰጠ ማንኛውም የገንዘብ ችሮታ/መስዋዕት (መባእ) ገቢ  በተዋህዶ ቤተክርስትያን ጳጳሱ በዮፍታሔ ዲሜጥሮስ በኩል ለኢሳያስ መንግስት ስራ ማስኬጃ እንዲሆን ለምጣኔ ሐብት ሃላፊው ለሐጎስ ገብረህይወት (ኪሻ) ገቢ እንዲሆን ትእዛዝ ተላልፎ በትእዛዙ መሰረት ገቢ ይደረግ ነበር።
የቤተክርስትያናት እና ገዳማት መስዋእት በመንግስት ትዕዛዝ መውረስና (ናሺናላይዝ) በየጊዜው የሚሰበሰበው መስዋእት(ገቢ) በመንግሰት ቁጥጥር እንዲሆን ያደረገ መንግስት በዓለም ተስምቶ ታይቶ ያልታወቀ፤ እንዲህ ያለ ጉድ የሰማነው የመጀመሪያ ጀሮአችን  በኢሳያስ መንግስት ጊዜ ብቻ ነው። ይህ ብቻ እንዳይበቃው፤ በየገዳማቱ በክብር ተጠብቀው የነበሩ ቅዱሳን ጥናታዊ መጽሐፍትና ቅርሳቅርሶች በስርዓቱ እውቅና እንዲሸጡ ተደርገዋል።
ለእጣን እና ለሻማ መግዣ እንዲያገለግል ከድሃ ሕዝብ የተጠራቀሙ ሳንቲሞች የሚዘርፍ መንግስት ከዘመነ ኦሪት ጀምሮ እስካሁን ድረስ እንዲህ ያለ ስራ የሰራ መንግስት በታሪክ ሰምተን አናውቅም። 

ኦ! ማርያም!

በ2005 አንድ አዛውንት አባት ባንድ ሃዘን ቤት ውስጥ ሄደው ሲያዳምጡት የነበረው ስርዓቱን በሚመለከት የሰዎች ጫጫታ፤ቅሬታና እና አለመደሰት አስመልክቶ ሃዘን ቤቱ ውስጥ ሰዎች ተሰብስበው “ኦ ማርያም!” እያሉ “ምህላ” ሲማለሉ ከሰሙ በላ እንዲህ አሉ፡
“እናንተ ሰዎች ምነው ፤ ምን ነካችሁ! ምንድነው እስከዚህ የሚያስተክዛችሁ? አያችሁ፤ እኛ እኮ ለነዚህ ልጆቻችን በተለይ ለመሪያቸው ለኢሳያስ አፈወርቂ  “እናታችን ኪዳነምህረትን” ወደ ቤት ገርግስ (አስመራ አካባቢ የሚገኘው ከፍታ/ተራራ ነው) ሄደን “ ኦ ማርያም ሆይ! እባክሽን እነኚህ ‘ጊንዳዕ’ ተራራ ላይ መሽገው የሚገኙት ልጆቻችን በተለይ መሪያቸውን ኢሳያስ አፈወርቂ ወደ ከተማ አንዲገቡልን በጸሎትሽ አማልጅን ብለን ለምነናት ነበር። በልመናችን መሰረት እሷም ልመናችንን ሰምታ የተለመነቺውን አደረገች። አሁን ምን አድርትሏታላችሁ? ይልቁንስ ማድረግ ያለብን ወደ እየ እምናምናቸው አድባራት በመሄድ “ኦ! ማርያም” እባክሺን እነዚህ ያመጣሺልንን እርኩሶች ወደ ነበሩበት ተራራ መሊሽልን ፤በተለይ ደግሞ መሪያቸውን ወደ ነበረበት ዋሻ ምልሰሽ ውሰጂው።እባክሽን እመቤቴ ሆይ ካሁን በፉት እንደሰማሽን ዛሬም ጸሎታችንን ሰምተሽ “ወደ እዚያው መሊሺልን”። ብለን ነው መጸለይ የሚገባን። አሉ።
በመቀጠልም፤ “ደግሞ እኮ ተጋዮች! ታጋዮች! እያላችሁ የምትጠሯቸው ታጋዮች ዛሬ ታጋዮች የሚባሉ በህይወት አሉ እንዴ!? የሉም እኮ! አራቱ ልጆቼ ታግለዋል። ሁለቱ ተሰውተዋል።አንዱ አካለ ስንኩል ሆኗል፤ አራተኛዋ ልጄም አባቶቻችን እና አያቶቻችን ሰምተውት የማያው ትን ገዳሪፍ ወደ ሚባለው የሱዳን መሬት የታገለችለት ነፃነት ኑሮ ዘግንኗት ወደ ስደት ሄዳ የወለደቻቸው  ልጆቻም እዚህ ጥላ አስመራ ውስጥ “ማይ አባ ሻውል”  ሳንቲሞችን ለመልቀም ቆሎ እና ማስቲካ ሲሸጡ ይውላሉ። ለዚህ ውጤት ነበር እንግዲህ ልጆቻችን ታግለው የተሰውትና አካለ ስንኩላን የሆኑት። ስለዚህ፤ታጋይ! ታጋይ! የምንለው ታጋይ በህይወት ሲኖር እንጂ በህይት የሌለ ነፃነቱ የተነጠቀ ታጋይ ማንሳት ፋይዳ የለውም። ይልቁንም ማርያም ካመጣጫቸው ዋሻ መልሳ እንድትመልሰልን መማጸኑ ይበጃል!” ብለው ከተናገሩ በላ ሲማለሉ የነበሩት ሀዘንተኞች መማለሉን አቁመው ድምፃቸውን አጠፉ።

የእሰር ቤት ብዛት

እንደ ኮሚኒስት ስርዓት ተከታይ መንግስታቶች ሁሉ ኤርትራ ያለው ስርዓትም ከትምህርት ቤት ይልቅ የእስርቤቶች ብዛት እጅግ ይበልጣል። እስከ 2011 ዓ.ም ድረስ ወደ 300 የሚያክሉ የተለያዩ እስር ቤቶች በየቦታው ነበሩ።አንዳንዱ እስር ቤት በገሃነም ዓለም ውስጥ እንጂ በዚህ ዓለም ይገኛል የማትላቸው በጣም አስፈሪ የሆኑ አስደንጋጭ እስር ቤቶች ኤርትራ ውስጥ አሉ።
ኢሳያስ ለእስረኞች ምህረት ያደርጋል ብሎ ማለት የማይደረግን መመኘት ነው። እንኳን እና የቅርብ ጊዜ እስረኞች ሊፈታ ይቅር እና ድሮ የታሰሩም አልፈታቸውም። ያውም ከነፃነት በፊት በትግሉ ጊዜ ታሰረው እስከ 2005 ድረስ 2ኛ እና 6ኛ ፖሊስ ጣቢያ ጉድጓድ እስር ቤት ውስጥ ታስረው የነበሩ እስረኞች የጣት ጥፍራቸው፤ የራስ ፀጉራቸው እና ፂማቸው እንዲላጩ ስለማይፈቅዱላቸውና እንደዚያ ሆነው ለአመታት ስለቆዩ ተጠግተህ ስታያቸው እጅግ የሚያስደነግጡ “ህቡአን” ወይንም በድሮ ዘመን ዋሻ ውስጥ በብሕትውና ሲኖሩ እንደነበሩ ባሕታዊያን ይመስሉ እንደነበር ያይን ምስክሮች ይናገራሉ።በጣም የሚያሳዝን ነው።ይህ አያያዝ ደግሞ የፈሪዎችና የቦጅባጆች አያያዝ ድርጊት እንጂ የኢሳያስ መንግስት እንደሚዋሸው የፍትህ እና የሕግ መንገድ የሚከተል ስርዓት የሚፈጽመው አይደለም።ለዚህ አምባገነን ምቾት “ብዙ ጀግና የትም ወድቆ መቅረቱ አንጀት የሚበላ ታሪክ ነው!” ነፃነት ላመጡለት ለነዚህ ጀግኖች ከእስር ቤት በነፃ ከማሰናበት ይልቅ እና ሃውልት አቁሞ በጀግንነታቸው ከመኩራት ይልቅ የሃይለስላሴን ሃውልት አፍርሶ አስመራ ከተማ ውስጥ የአሌክሳንደር ፑሽኪን መታሰቢያ ሓወልት ማቀሙ ከሚገርም በላይ የሚገርም ድርጊት  ነው። የኢሳያስ አስገራሚ እንቆቅልሽ ባሕሪ እና ማንነት ለማወቅ ሁሉም ያልተገለጡ ምስጢሮችን መቆፈር መጀመር አለበት።ሚስጥሮቹ በተቆፈሩ ቁጥር ለማመን የሚያስቸግር እውነታዎች ወደ መድረክ ብቅ ሲሉ እንኳን የዋህ ህዝብ ለታጋይም እጅግ ያስደነግጣሉ።

አምላኬ ሆይ ይችን እግር አብቅልልኝ

በትግሉ ወቅት የማውቀው አንድ እግሩ ያጣ ድሮ ጀግና ታጋይ ‘ፍያት’ በተባለ አካባቢ ተገናኝተን ብዙ ትዝታዎችን አንስተን ሰናወራ “ዋይ አነ እግረይ!” ወይኔ እገሬ! አለ። ወይኔ እገሬ! አንተ አምላኬ ምነው እባክህን ዛሬ ቀን እንደቸርነትህ ይች ያጣን እግሬን ብታበቅልልኝ!? እባክህን አብቅላት! ሲል እኔ ደግሞ “እንዴ ምነድነው የምተለው፤ ምን አይነት ልመና ነው የምትለምነው? እሱም “ልክ እንደመልህ!” አለኝ። ዛሬ ማታ ይህ አምላክ ይችን ያጣት እግሬን ብያበቅልልኝ በማለዳ “ወደ ተከዜ ነበር በርሬ የምገሰግሰው። በዚህ አገር ውስጥ ባሁኑ ሁኔታ ጫካ ገብተህ ሸፍት!ሸፍት! እንጂ ምንም ሌላ ነገር አይታየኝም። አይን አይኑን ትኩር ብዬ እያየሁት “እንዴ ታዲያ ለሽፍትነት እንዴት ዛሬ ተመኘሃት?” ስለው፡ “በሚገባ እንጂ! አዎን! ለምን አልመኘውመም? ሳሕል በረሃ የታገለንለትን እና የተነገረንን አሁን እዚህ ስንደርስ የት አለ? “ሁሉም እንደየ ችሎታውና ሁሉም እንደየ አቅሙ” ሲባልልን የነበረው  የኮሚኒሰቶች ትምህርት፤ የልጆች ጨዋታ፤ ሆኖ ነው ያገኘነው። እስኪ ልብ ብለህ እንደሆነ የኔ ጓዴ! በአንፃሩ የእስር ቤት ህንጻዎች በገፍ ሲገነባ እኮ  ነው እያየነው ያለነው።” ብሎ በሃዘን እና በምሬት ተክዞ መለሰልኝ። ኤርትራ ዛሬ ውቅያኖስ ውስጥ መሪ እና ኮምፓስ እንደሌላት መርከብ ሆና ከወዲያ ወዲህ እየዋዠቀች ትገኛለች።  አሳዘኝ ገድል!

ምፅዋ ላይ የስዓት እላፊ

አንዳንድ በህግደፍ ኮሚኒስታዊ ትምህርት ሕሊናቸው የታጠቡ የህግደፍ ወጣት ካድሬዎች ስላለፈው ትግል ታሪክ እና ስለ  የኢሳያስ ማንንት ቅንጣት ታህል አያውቁም። ለዚህም ነው “የናቅፋ አንበሳ ብለው የሚዘፍኑለት”።ናቅፋ ውስጥ ማን አምበሳ እንደነበረ ግን ታሪክ ቀስ ብሎ ወቅቱ ጠብቆ ይነግረናል። እስካሁኗ ደቂቃ ድረስ ኢሳያስ አሽከሮቹ የደበቁት ብዙ አሳፋሪ ገበናዎች አሉዋቸው። እነኛ እውነታዎች ቀስ በቀስ ወደ ገሃዱ ብርሃን እየወጡ ናቸው።ኢሳያስ ዛሬ ከኤርትራ ባላባቶች እና ሕዝብ ጋር በደምብ ተዋውቋል። ሕዝቡ የሰውየው “አጥፍቶ መጥፋት እቅዱ” እና ማንነቱ እራሱ በጐነጐነው መሰሪ ተንኰሉ በግልፅ እያወቀው መጥቷል።
ኢሳያስ ምፅዋን የግል መደበቂያው አድርጎ የመረጣት የግል ከተማው ነች። ቀይ ባሕር ዳርቻ ላይ ያለቺው ምፅዋ “አድኒኝ” ብሎ እጅ የሰገደላት ከተማ ሆናለች።እንዲሸሸግባት የመረጣት ይች ከተማ በደምብ እንደትጻዳ አድርጓታል። “ነፃ አውራጃ” በሚል የዘመቻ ሽፋን ስም ሰይሞ እራሱ ቆሞ በቡለደዘር እንድትጠረግ አድረጓል። በዚህ ዘመቻው ሕዝብን ከማቋቋም ይልቅ ማፈናቀል መመሪያው ያደረገው ኢሳያስ አፈወርቂ ‘ምፅዋ ኗሪዎች ላይ ያደረሰው ፍዳ አሰቃቂ ነበር”። ለዚህም ነው “በመጥረጊያ በደምብ አድርጐ እራሱ ቆሞ የጠረጋት” የሚባልለት።
ድሆች የሚኖሩበት መኖሪያ ቤቶች በቡልዶዘር ማፍራረስ “ከዚህ ከተማ ወጥታችሁ ጥፉ!” ብሎ ኗሪዎችን አስቸኳይ ትእዛዝ በማስተላለፍ በኤርትራ ዜጎች ላይ አሳዛኝ ድርጊት ፈጽሟል። እዚህ ነው አገራችን እና መኖሪያችን! እንዴ! ወዴት እንድንሄድ ፈለጋችሁን? ብሎ ሕዝቡ ሲጠይቅ “ይህ አገራችሁ አይደለም ወደ እየ አገራችሁ ሂዱ” ብላ  ወ/ሮ ፋና ተስፋማርያም መለሰችላቸው።
ኗሪውም፡ እንዴ “ ታዲያ ለምን ኢሳያስ እና ወ/ሮ ፋና ወደ የትውልድ አገራቸው ለምን አይሄዱም? ምን ያለ አበሳ አድርገን ነው እንዲህ ያለ ፍዳ በላያችን የሚፈጸመው? የወላጆቻችን እና የቅድመ አያቶቻችን መቃብር እና መኖሪያ ቤቶችን የሚያፈርስ ምን እሚሉት ስርዓት ነው የመጣብን! ሲል ምሬታቸውን ገለጹ።
በጣም የሚገርመው ደግሞ አንድ ሓላፊ “እነኚህ የድሮ የሕዝብ ጉዳይ አስፈጻሚዎች/ክፍሊ ሕዝቢ ታጋዮች የነበሩ የዛሬዎቹ “አስተዳዳሪዎች” ፍትሕ የሚባል ነገር አያውቁም እና “ጥጃ ራስ” ወደ ተባለው የአካባቢው የሰራዊት ሃለፊ ሄዳችሁ “አቤት” በሉ ሲላቸው። “ወይ ጉድ! በከፍተኛ ቦታ የተቀመጠቺው “ያሕያ ራስ” ያልሰጠቺን ፍትህ ቁልቁል ሄደን “ጥጃ ራስ” ፍትህ ይሰጠነል ማለት ድካም ነው አሉት ይባላል። የአህያ ራስ (ርእሲ አድጊ) ብለው በቅጽል ስም የሚጠሯት (የፊቷ ቅርፅ የአህያ ይመስላል በሚል ነው ) ባለስልጣን በወቅቱ ከወ/ሮ ፋና ሌላ የምፅዋ አስተዳዳሪ የነበረቺው የኢሳያስ ባለሟል ወ/ሮ እዝግሃርያ የምትባለዋን ነው።
በዚህ ውሳኔ መሰረት ምፅዋ ከተማ ውስጥ የነበሩት ባሪስታዎች (ቡና ቤት ሰራተኞች)፤ ድሆች “ዊዓ” ወደ ተባለው በረሃማ ስፍራ ተወሰዱ። የምፅዋ ሆቴሎች/ባር ለማንኛውም ሰው ሙሉ ሌሊት ክፍት የነበረው ያኔ 11 ሰዓት ከምሽቱ ስዓት እላፊ ተላልፎ ለማንም ሰው ዝግ ናቸው። ቢራ፤ኮካ ኮላ እንደፈለግከው አይገኝም። አልኮሆል እና የፍራፍሬ ጭማቂ አይታሰብም። ከግማሿ ሌሊት በላ የኢሳያስ ልዩ ወታደሮች በስተቀር አንድም ዝር የሚል ሰው የለም። ከተማዋ የሙት ከተማ ትመስል ነበር።
በጣም የሚገርመው ነገር በዛች በሙት ከተማ በውድቅት ሌሊት ኢሳያስ አፈወርቂ ከመኖሪያ ቤቱ ወጥቶ ብቻውን እንደ ጋኔል “ስጋለት ቀጣን” በምትባለዋ ጥርጊያ እየዞረ እንደሚታይ እንሰማ ነበር። ለዚህም ነበር ምፅዋ ውስጥ 11 ሰዓት ላይ ሰዓት እላፊ በማወጅ ማንም ሰው በእግርም ሆነ በመኪና መዞር አንደማይፈቀድ ትእዛዝ ያስተላለፈው።
ሰው እንዳይዘዋወር አግዶ ዛሬ እንደሌሊት ወፍ ብቻውን የሚዞረው  ኢሳያስ መጨረሻ ላይ ወጣቱ ኑሮ አስመርሮት ወደ ስደት ሄዶ በአረመኔ በደዊን አረቦች እና ግብፆች “ሲናይ” ምድረበዳ ሰሃራ ውስጥ እየታፈነ ኩላሊቱ እና ጉበቱ  ሳይሞት እንደ በግ በገመድ ተጠፍሮ በሽፍቶች እየታረደ ለገንዘብ አትራፊ ነጋዴዎች እንዲሸጥ ለሞት አብቅቶታል። ኤርትራዊ ማለት ኩራት እንዳልነበረ ሁሉ ዛሬ “ኢትዮጵያዊ” ነኝ እያለ ኤርትራዊ ወደ ስደት ዓለም ሄዶ ስሙን በኢትዮጵያዊ ዜጋ ይመዘገባል።ስለዚህ ኢሳያስ እና ቡድኖቹ ኤርትራን ለማፍረስ ድሮ ወደ ትግሉ ሲገባ የተመለመለበት ድብቅ ተልእኮው እውን እያደረገው እንደሆነ አሁን አሁን ግልፅ እየሆነልን መጥቷል።

ቤተክረስትያን ላይ የፈጸመው ድብቅ ወንጀል

በመጀመሪያ የነፃነት አመታት ወቅቶች ላይ የላካቸው ኮሚኒስት የክረስትና ትምህርት ያላቸው ሰባኪያን አባሎቹ በድብቅ ወደ ማሕበሩ በማስሰረፅ፤ በቅድስት ስላሴ (ዕዳጋ ሓሙስ) እና አስመራ “እንዳ ማርያም” ቤተክረስትያን ቅዱሳት መጽሐፍት በእሳት እንዲቃጠሉ አድርጓል።
ገዛ ባንዳ ያለው “መድሃኒአለም ቤተክረስትያን” ምእመናን/ሕዝቡ በሚሰግድበት እና በሚጸልይበት ቅጥር ግቢ ውስጥ ደግሞ በብዛት “ኮንዶም” በመበተን አስጻያፊ ድርጊት ተፈጽሟል። በየገጠሩ እና አካባቢው የተጠራቀመ ለሻማ እና ለጧፍ መግዣ የተለገሰ መስዋእት እንዲዘረፍ ተደርጓል።ይህ “ዶሮ ጭራ የምታገኘው” ተንኰል ከማን የታዘዘ እንደነበር ሁሉም ሰው ስለነቃበት ይህ ኩነኔ እና አስነዋሪ ድርጊት ከፈጸሙ በላ ይቅርታ ጠይቀው “ድርጊቱ” በምስጢር እንዲያዝ እንደጠየቁ እናውቃለን።

ንቅዘት

በስርዐቱ ውስጥ ያልታየ ጉድ የለም። ወታደራዊ መኳንንት ፤ጀኔራሎች ቢያንስ ከ2 እስከ 3 ሚሊዮን ዶላር ካፒታል እንዳላቸው ይገመታል። አገሪቱ የራሳቸው የኢሳያስ እና ጥቂት ባሪያ ጀኔራሎቹ ንብረት ሆናለች። የወርቅ ዘረፋ፤ የጦር መሳሪያ ዘረፋ፤ እና ጥቁር ገበያ ንግድ፤በጠቅላላ የኢኮኖሚ ምህዋሮች በቁጥጥራቸው ስር ነው።የንግድ ፈቃድ ሲፈልጉ ይሰጣሉ ካልወደዱህ ይከለክሉሃል። መላው አፍሪካ ድረስ ፤ጫድ ሱዳን መካከለኛው አፍሪካ …ወሳጅ እና አስተላላፊ አዋቅረው  ከማፊያ በባሰ ምስጢራዊ አሰራር በመንግሰት ሽፋን ሁሉንም ዓለም አዳርሰውታል።
እያንዳንዱ ፓስፖረት ከ1000 (አንድ ሺሕ) ዶላር የሚደርስ 30 ሺህ ፓስፖርት ለተለያዩ ሕገ ወጥ ዜጎች ኤርትራዊ የሚል ይሸጣል። አስመራ ውስጥ የመሸጉ የኢትዮጵያ ተቃዋሚዎች ሳይቀር ሲያስፈልግ ባንዳንድ ቦታዎች በዚህ ሕገ ወጥ ፓስፖርት ነው የሚንቀሰቃሱት።
ኩወይት ውስጥ ፡ “ብዱን” ተብለው የሚታወቁ ኩዌት ውስጥ በዝርፍያ፤ግድያ፤ጥቁር ገበያ፤ሓሺሽ በማዞር በመሳሰሉ ወንጀሎች በመፈጸም የታወቁ በዝቅተኛ ዜጋ የሚታዩ የኩዌት አረቦች በገንዘብ እየተሸጠላቸው “ኤርትራ” የሚል ፓስፖርት ይዘው የትም በመዞር ወንጀል በመፈጸም ሲያዙ የኤርትራዊያኖችን ዜጎች ስም በወንጀል ተጽፎ እንዲመዘገብ ሆኖ ድርጊቱ የፈጸሙት “ኤርትራዊያን” ናቸው ይባላል።

ባር ገብሩ አስራት

የኢሳያስ ጀኔራሎች እና ጥቂት አሽከሮቹ የሚጠጡት መጠጥ እጅግ ውድ የሆኑ አልኮሆል መጠጦች እና ማ ይመገባሉ። በ2004-2007 የጭንቅ ወቅት ተብሎ በሚታወሰው ጊዜ፤ የኢሳያስ ጀኔራሎች “ብሉ ናይል” በመሳሰሉ እና ከፍተኛ ውድ ሆቴሎች እና መጠጥ ቤቶች ውስጥ በመግባት 4 ወይንም 5 ሰዎች ሆነው ለአንድ ጊዜ 22,000 ናቕፋ (የኤርትራ ገንዘብ) ከፍለው ሲጠጡ ማየት በጣም አስገራሚ ዜና ነበር። በወቅቱ 3 “ብሉ ሌበል” የተባለው ዊስኪ ጠርሙስ እያንዳንዱ ጠርሙስ በ7000 ማለትም 21,000 ናቕፋ እና በዚህ ላይ ውድ የምግብ ዋጋ ተደምሮበት ከ22ሺህ ናቕፋ በላይ በመክፈል ሲዝናኑ ነበር።
ከዚያ ወዲያ ነበር  አንዳንድ ሰዎች “ብሉ ናይል ሆቴልን” “ባር ገብሩ አስራት” ብለው ይጠሩት የነበር። ምክንያቱም እንደሚታወሰው በባድሜ ጦርነት በፊት ኢሳያስ ባድሜን ሲይዛት ገብሩ አስራት የትግራይ ክልል አስተዳዳሪ በነበረበት ወቅት “የተከፈለ ዋጋ ይከፈል! የተከፈለ መስዋእትነት ይከፈል! የሚጠይቀወን ዋጋ ሁሉ ከፍለን ባድሜን እናስመልሳለን!” ብሎ ተነጋሮ ስለነበር፡ የብሉ ናይል መጠጥ እና ምግብ “ወድ ዋጋነት” ለማሳየት ነው። ምክንያቱም ለተራ ሰው ውድ ቢሆንም እንኳ  ብሉ ናይል የጠየቀው ዋጋ ቢጠይቅም የኢሳያስ ጀኔራሎች “የተከፈለው ገንዘብ ከፍለው በውድ ዋጋ ይጠጣሉ፤ ለማለት ነበር ፤”ባር ገብሩ አስራት” ብለው “ብሉ ናይልን” የሚጠሩት።

ተሰነይ ውስጥ ያለው አረመኔው መርማሪ

ተሰነይ ውስጥ እስረኞች ምን እንደሆነ የማይታወቅ “ሽንት የሚመስል ነገር”  በገረወይናይ (ጀሪካን/ቆርቆሮ) ተሸክመው ከእስር ቤታቸው ይወጣሉ። በየሌሊቱ የሚቀበር ሰው አለ። ማን ነው? ወንጀሉ ምንድነው? የሚታወቅ ጉዳይ የለም። አንዳንዶቹ በደረሰባቸው ከባድ ድብደባ ነው የሚሞቱት።
“ሚሻ” በሚል የቅጽል ስም የሚጠራ መርማሪ እስረኛ በያንዳንዷ ሌሊት ሲመረምር አንድ እስረኛ ደብድቦ መግደል አለበት። ይህ ሰው ቀን ቀን፤ በዛው እስር ቤት ውስጥ ተኝቶ አንቅልፉን ያስተናግዳል። የሚተኛበት ክፍል ደግሞ ኰሎኔል ዮናስ ከተባለው የዞባ 1 የስለላ ሃላፊ ጽ.ቤት ውስጥ ልዩ የመኝታ ክፍል ተሰጥቶት ነው እዛው የሚተኛው።  ሌሊት ሌሊት ደግሞ እንደ ሞገደኛ የመንደር ጅብ “ዜጎች” ሲደበድብ እና ሲገድል ያድራል። በሂትለራዊው ኢሳያስ ስርዓት ኤርተራዊ ዜጋ ያገኘው መከራ ተነግሮ አያልቅም። ታዲያ ይህ ሁሉ ሺህ ጀግና ታገይ ለዚህ ነበር ሎጋ ሕይወቱ የሰጠው? አካለ ስነኩል ሆኖ የቀረው? ለመስዋእቱነቱ ካሳ “ረሃብ፤ግፍ ርሸና ፤ፍትሕ አልባ እና ሰቀቀን” ከሆነ “ብለሽ ታሕሪር! ነው (በከንቱ  የቀረ ነፃነት) ቢባል አያስገርምም። ይላል ደራሲው። ትግርኛ የምታነቡ ሰዎች መጽሐፉን ገዝታችሁ ማንበብ ይኖርባችል፤፡ አድራሻውም ይሄው alenakoena@gmail.com የአድራሻ ችግር ከገጠማችሁ መልሳችሁ ብትጠይቁኝ ኢንተርኔት ገበያ ውስጥ የት አንደምታገኙት ልጠቁማችሁ እችላለሁ። አመሰግናለሁ ይህ ጽሑፍ ወደ አማርኛ የተረጐመው” ጌታቸው ረዳ” www.ethiopiansemay.blogspot.com
getachre@aol.com (408) 561 4836